Home ቤተ ክርስቲያናችን

ቤተ ክርስቲያናችን

ቤተ ክርስቲያናችን

በቦልቲሞር ሜሪላንድ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተክርስቲያን እንደ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ በ1993 (2001) በኮሎቢያ,ሜሪላንድ(Columbia,MD)  በአባ ፊሊጾስ መሪነት በፆምና በፀሎት ተመሠረተ። ለመጀመሪያ ጊዜም (Elkridge) በሚገኘው የኮፕቲክ ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ስርዓተ ቅዳሴ ፀሎት በሚገባ ተካሄደ። ለማስታወስ ያህል በመቅደሱ ዙርያ በፀሎት የተራዱን አባ ፊሊጾስ ፣ ቀሲስ ሰለሞን ዲ/ን ዮርዳኖስ እና በወቅቱ ዲ/ን የነበሩት አሁን ግን ቤተክርስቲያናችን የክህነት የሚያገለግሉን አባታችን ቀሲስ ዘነበ ነበሩ።  በእግዚአብሔር መልካም እና ቅዱስ ፈቃድ  የዓጋእዝተ ዓለም ቅድስት ሥላሴ ፅላት ከኢትዮጵያ ተዘጋጅቶ በወቅቱ አባ መላኩ የአሁኑ ግን  የጵጵስና ማዕረግን በተቀበሉት ብፁዕ አባታችን አቡነ ፋኑኤል እጅ መጥቶ ጥር 7/1993(Jan 15/2002) ዕለት ብፁዕ አባታችን በአቡነ ይሥሀቅ ተባርኮ በወቅቱ እንገለገልበት በነበረው 208 S Broadway, Baltimore, MD ላይ በሚገኘው ቤተክርስቲያን በደማቅ አከባበር ፅላቱ በክብር ወደ ማረፍያው ቤተመቅደስ ገብቷል። የቅድስት ሥላሴ ቤተክርስቲያን በአዋጅ አገልግሎት ከዚህ ጊዜ  ጀምራ ለምዕመናን ክፍ  ሆና በእለተ ሰንበት ስርዓተ ቅዳሴውን ፀሎት ምህላውን ስትደርስ ቆይታለች። የተለያዩ  ካህናት አባቶች ካህናት ዲያቆናት በመፈራረቅ ሲያገለግሉ ቆይተዋል እስካሁን ድረስ። የቅድስት ሥላሴ ረድኤት ከእኛ ሳይለይ በእርሱ ፈቃድ እንሆ እስከ ዛሬ አገልግሎት ተቋርጦ አያውቅም።

ከዘጠኝ ዓመት የአገልግሎት ዘመናት በኋላ ማለትም August 2011 ላይ በተከሰተው የአየር መዛባት ምክንያት እንገለገልበት የነበረው  ቤተክርስቲያን ጣሪያው በመጎዳቱ አሁን ወዳለንበት 1532 East Fort Ave Baltimore, MD ቤተክርስቲያን ለመዘዋወር ተገደናል። አሁን በምንገለገልበት ቤተክርስቲያን በተቻለ መጠን አገልግሎታችን  አስፍተን አንዳች ሳናጎድል በዕለተ ሰንበት በአጥብያው የሚገኙ ምዕመናን ሁሉ ከቅዳሴው በረከት የሚሳተፋበት፣ በምህላ እግዚአብሔርን የሚለምኑበት፣ልጃቻቸው የሚማሩበት የሚቀደሱበት በማድረግ ላይ እንገኛለን።እግዚአብሔር አምላክ ቢረዳን በቅርብ ጊዜ ውስጥ የራሳችን የሆነ ህንፃ ቤተክርስቲያን በመግዛት ለአጋእዝተ ዓለም ቅድስት ሥላሴ ፅላት ቋሚ ማረፍያ በማዘጋጀት አገልግሎታችንን በተጠናከረ ሁኔታ እንደምንቀጥል እናምናለን። ለዚህም የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት የቅዱሳን መላእክት ጠባቂነት የፃድቃን የሰማእታት ተራዳኢነትና የሥላሴ ልጅነት አይለየን። አሜን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር


UPCOMING EVENTS

    There are no upcoming events at this time.